20/05/2026
መልካም ዜና ከአውሮፓ ህብረት ለኢትዮጲያውያን ✅
ምክር ቤቱ እ.ኤ.አ. በ2024 በኢትዮጵያ ላይ ጥሎት የነበረውን የቪዛ ገደብ ለማንሳት ትናንት በይፋ ወስኗል። በተሻሻለው ህግ መሰረት፥ በማዕቀቡ ወቅት 45 ቀናት ይወስድ የነበረው መደበኛው የቪዛ ማስተናገጃ ጊዜ ወደ 15 ቀናት ዝቅ ይላል። በተጨማሪም መስፈርቱን የሚያሟሉ ኢትዮጵያውያን ተጓዦች በድጋሚ የባለብዙ መግቢያ (multiple-entry) ቪዛ ማግኘት ይችላሉ።
ይህ ውሳኔ የኢትዮጵያ ዜጎች የሼንገን (Schengen) ቪዛ በቀላሉ ማግኘት እንዲችሉ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል። ውሳኔው በምክር ቤቱ በይፋ መጽደቁን ተከትሎ፥ በሁሉም የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት የቆንስላ አገልግሎቶች ተግባራዊ መሆን ይጀምራል።
የአውሮፓ ህብረት ምክር ቤት (The Council of the European Union) ኢትዮጵያ ህገ-ወጥ ስደተኞችን እና የወንጀል ፍርድ የተፈረደባቸውን የውጭ ሀገር ዜጎችን መልሶ ለመቀበል የሚያስችሉ እርምጃዎችን ለመተግበር በመስማማቷ ምክንያት በኢትዮጵያውያን ላይ ጥሎት የነበረውን የቪዛ ገደብ አንስቷል። ማዕቀቡ የተጣለው የአዲስ አበባ መንግስት ስደተኞችን መልሶ የመቀበል ሂደትን በተመለከተ ያለውን ትብብር እንዲያሻሽል ግፊት ለማድረግ ሲባል የአውሮፓ ህብረት የቪዛ ህግጋት ከፊል ክፍሎች እንዲታገዱ ተደርጎ ነበር።