17/08/2026
ጎረቤቷ ለሚስቱ አዲስ መኪና ገዝቶ ሲሸልማት በትኩረት ስትከታተል ቆይታለች። ያን እይታዋን እንደጨረሰች፣ ወደ ሥራ ለመውጣት የሚዘጋጀውን ባለቤቷን በአይነ ቁራኛ ትመለከተው ጀመር።
«ለቤት ወጪ የሚሆን ገንዘብ ስጠኝ» አለችው።
እርሱም እንደተለመደው፣ «ትናንት የሰጠሁሽ 300 ብር አለቀ እንዴ?» ሲል ጠየቃት።
ኑሯቸው የከፋ ባይሆንም፣ በውስጧ የተቀሰቀሰው የፉክክርና የመቀናት ስሜት አዕምሮዋን ወጥሮት ነበር። በሌላ ጊዜ ቢሆን በቀላሉ የምታስረዳውን ነገር፣ ዛሬ ግን ንዴት አነቃት።
«በዚህ በጋለ የኑሮ ውድነት 300 ብር ሰጥተህ በሱ ትነዘንዘኛለህ?» አለችው በቁጣ።
ባል ግራ በመጋባት አያት። ኪሱን ደባብሶ ያገኛትን የመጨረሻ 200 ብር አውጥቶ ሰጣትና ምንም ሳይናገር ወጣ።
ደመወዙ 13 ሺህ ብር እንደሆነ ታውቃለች። ለዚች በመጋረጃ በተከለለች ትንሽ ቤት 7 ሺህ ብር የቤት ኪራይ ይከፍላሉ። የታክሲ ወጪው 1,500 ብር ቢሆንም፣ አብዛኛውን ጊዜ ወጪ ለመቀነስ በእግሩ ወይም በሕዝብ ባስ ይጓዛል። ቀሪዋን ብር ደግሞ ተማክረውና አቅደው ነው የሚያወጧት፤ እርሷ የማታውቀው የተሸሸገ ብር የለውም። አንዳንዴም ደመወዝ አልቆበት ወይም ብድር ከብዶት ግራ ሲገባው፣ እርሷ ከወጪ ቀናንሳ የቆጠበቻትን አውጥታ በመስጠት ከጎኑ ትቆም ነበር።
ቤታቸው በሰላምና ፍቅር የተሞላ ነበር። እርሱ ግን አሁን በምን እንዳስከፋትና ምን እንደበደላት ግራ ተጋብቷል፤ ምክንያቱ ባልገባቸው አጋጣሚዎች ላይ እንደዚህ ስትናደድበት ያጋጥመዋል።
እርሱ ከወጣ በኋላ፣ የንዴቷ ትፋት በርደድ ሲል አንድ እውነት ከአእምሮዋ ዘልቆ ገባ፦
«በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምታዩትን የተጋነነ ህይወት እያያችሁ ትዳራችሁን አትበድሉ። በማስታወቂያ ወይ በብድር በሚታይ ጊዜያዊ ድምቀት የራሳችሁን እውነተኛ ህይወት አትመዝኑ፤ አታወዳድሩም።»
ይህ እውነት ውስጧን ሲሞግተው አገኘችው። «ቢኖራቸውና ቢሰጣጡ የነሱ ህይወት ነው! እኔስ ቢሆን ይህ ይገባኝ ነበር? ባለው አቅም ልክ ደግነቱንና መልካምነቱን የማያጉድልብኝን ሰው ማሳነሴና ቤቴን ማመስበሴ ትክክል ነበር?» ስትል ራሷን ጠየቀች።
ፀብዋ ለነሱ ከሰጣቸው ፈጣሪ ጋር ይሁን ወይስ ያለውን አቅሙን ሁሉ ከሚጥረው ባለቤቷ ጋር? ግራ ተጋባች።
ወደ አእምሮዋ ስትመለስ ግን የሰራችው ስህተትና የባሏ ሁኔታ አሳሰባት። «አይ! ያለውን አይደል እንዴ የሚሰጠኝ? አሁንስ ያችን ብር ሰጥቶኝ በእግሩ ይሄድ ይሆን ወይንስ ከሰው ተበድሮ?» እያለች በፀፀት ታስብ ጀመር።