11/01/2026
☸️የጉራጌና የከንባታ ባላባቶች አቤቱታ🔯
►►►►►►►►►►►►►►►►►►►
#በዚያ ወራት የሹም ሽሩ ሥራ ሁሉ ካለቀ በኋላ አንድ ቀን ወደ ምኒስትሮች ክፍል የምክር ቤት ስለተጠራሁ ሄድሁ፤ እንደኔውም ምኒስትሮች ያልሆኑ ሌሎችም ጥቂቶች
መኳንንት ነበሩ ፤ ከምኒስትሮቹም ጋር ወደ አስራምስቱ እንሆን ነበር፡፡ ወደ እተዘጋጀውም ስፍራ ገብተን እንደተቀመጥን ጸሐፌ ትዕዛዝ ወልደ መስቀል የተጠራንበትንና የተሰበሰብንበትን ጉዳይ በዝርዝሩ አመለከቱ፡፡
#ነገሩም #በጉራጌና #በከንባታ ወገን ያለው አገር ባላባቶች ባንድነት ሆነው አቤቱታ ላስታወቁት ጉዳይ ነበረ፡፡ቃሉም ‹‹እንደመሬቱ መጠን ለመልከኛውና ለሻለቃው የሚከፍለው የገባሩ ግብር ጥንት #ትንሽ ነበር፡፡ በየጊዜው የሚለዋወጠው የሻለቃ ሁሉ ግን አንዳንድ ነገር እየጨመረ ግብሩን ሁሉ #አሳድጐብን አሁን ብዙው ገባር #መገበር አቅቶት መሬቱን እየተወ #ተሰደደ፡፡ የዚያንም የተሰደደውን ገባር ግብር፣ እኛን #ባላባቶቹን #የግድ ገብሩ ብለው ያዙን፡፡የተሰደደው ገባር እየመኳንንቱ #የወላስማና #የጉልት መሬት ነው የገባው፡፡ይኸውም የወላስማና የጉልት መሬት የመንግሥት ግብር ብዙ ስለሌለበት እየተስማማ እየሄደ እርቦ አራሽ ሆነ፡፡ ለሄደውና ለሚሄደው ሁሉ #የስንቱን ገባር #ጠፍ መሬት ገብረን እንዘልቀዋለን፡፡ የሄደውንም ገባር ከሄደበት ተከታትለን እያወጣን በግድ ለመመለስ አንችልም፤ ባለጉልቱም ይከለክለናል፡፡ ስለዚህ አጥብቀን ተቸግረናልና፤ጠፉን መሬት ቢፈልጉ ገባሩ ጥሎት የሄደውን እናስረክባለን፡፡ በሄደው ገብሩ ተብለን እንዳንያዝ ደግሞም አሁን ያለውም ጨርሶ እንዳይጠፋ በየጊዜው የሻለቃና መልከኛ ያሳደገውና የጨመረው ግብር እንዲፋቅልን እናመለክታለን፤» ብለው በየጊዜው የተጨመረውንም ግብር በዝርዝሩ አጽፈው የሰጡትን ደጋግመው አንበው «ይኸን እንድታስቡበትና እንድትመክሩበት! ስለዚሁም የወሰናችሁትን እንዳውቀው ብለዋል ጃንሆይ» ብለው አመለከቱን፡፡
#ነገሩን ሰምተን ጥቂት ዝምታ ከሆነ በኋላ አንዳንዶች መኳንንት መናገር ጀመሩ፡፡ እነሱም የበላተኛውን ወገን፣ የመልከኛና የሺአለቃውን አበል ለመንካት የተጨመረውንም ግብር ዝቅ ለማድረግ እጅግ ፈርተው መልከኛው ደግሞ
አበላችንን ከለከላችሁ ብሎ ይነሳብናል! የሚያስቸግር ነገር ነው» እያሉ ተናገሩ፡፡ደግሞ ጥቂቶቹም፣ «መሬቱን እየለቀቀ የሚሄደውን ገባር ያው መልከኛው እየፈለገ እየተከታተለ እየያዘ ይመልሰውና ያስገብረው! በያንዳንዱ አገርስ እንደዚሁ ያለ ደንብ አለ የለሞይ፡፡ በንደዚህ ያለው ባላባት መያዙ ይቅር» አሉ፡፡
#እኔም በተራዬ ሁሉንም ካዳመጥኩ በኋላ ነገሬን ስጀምር ሁሉም ዝም ብለው አዳመጡኝ፡፡ የተናገርኩትም #በሐረርጌ ወገን ያለው ገባር አስተዳደሩ ከዚህ ከተነገረው ልዩነት ስላለው መጀመሪያ የዚያን አኳሆን ነበር፡፡ ‹‹በሐረርጌ ገባር መሬቱን ጥሎ ቢሄድ መልከኛው እራሱ መሬቱን ቢያርሰው ወይም ለሌላም አራሽ አጋዝቶም ቢሆን የሚገኘውን (ይበላል) ይወስዳል እንጂ ገባር አልችልም ካለ እንኳን ተሰዶና እዚያውም አገር ላገር አስታውቆ ለቆ ቢቀመጥ የሚነካው የለም፡፡ የተወሰነውም ዓመት ሳይደርስ እንኳን ወደ መሬቱ ለመመለስ ፈልጐ በፈቃዱ ቢመለስ ገብቶ አለችግር መያዝ
ይችላል፡፡ስለዚህ ሰው የሚገብረው ለኑሮውና ለትዳሩ ሲል መሬት ይዞ፣ ቤት ሰርቶ፣ሚስት አግብቶ፣ ልጅ ወልዶ፣ ለተቀመጠበት እንጂ! የማይችለውን ዕዳ ሊከፍልበት
አደለም፡፡ ደግሞስ ይኸንኑ መሬቱን ዕዳውን አልችልም ብሎ ደህይቶ ቢሰደድ የግድ እየተፈለገ የሚያዘው ምን ባደረገ ነው? እስኪ እራሳችን እናስበው፡፡ ሰው የሚወደውን
ቤቱን፣ እኖርበታለሁ ያለውን እርስቱን፣ እንዲኖር የሚረዳውና የሚደግፈው ዳኛ በማጣት ይኸው በየጊዜው የተጨመረበትንና ያደገበትን ጽፎ አቅርቦልን እናያለን፡፡ይኸን ያለ መንግሥት ፈቃድ የተጨመረውን ለመቀነስና ለማሻሻል መከራ መስሎ ይታያችኋል፡፡ በላተኛውን በመፍራት ከዚህ ለማዳን የማይቻል ሲመስላችሁ ድኃውን ከተሰደደበት አብርሮ መያዝና የግድ ገብር ማለት ትልቅ የግፍ ግፍ ነው» ብዬ «ይልቅስ እኔ አሳቤን ላመለክታችሁ የምሻው ከተናገርኩ በስተኋላ ቀጥዬ፣ እውነተኛው ነገር፣ ለመንግሥቱም ሆነ ለባላገሩ ታላቅ እንቅፋት ሆነን ለማሻሻል፤ያስቸገርነው፣ እኛና እኛን የመሰለው ሹማምንት ሁሉ ነን፡፡ ምክንያቱም ከመንግሥት ደሞዝ እንቀበላለን፡፡ አገርም እየገዛን የገባሩን ግብር እንወስዳለን፡፡ ደግሞም በዚሁ ላይ ብዙ ሰፋፊ መሬት እርስት እያልን እየያዝን መቶውን ጋሻ ባምስት ሸማ፣ አምሳውን
ጋሻ በሦስት ጉንዶ ማር፣ እየሆነ ብዙውን ሰፋፊ መሬት ሁሉ ያለ ግብር ይዘን እያወክን ባንድ ወገን በዚህ አኳሆን የመሬቱ ግብር ሁሉ እየጐደለ፣ በሌላው ወገን ደግሞ በገባሩ ላይ በመጨመሩ ሊኖር አቃተው፡፡በሌላው መፍረድ እንድንችል እስቲ መጀመሪያ በራሳችን እንፍረድ፡፡ ሌላው ነገር እንኳን ለጊዜው ቢቆይ እርስት ብለን ያለ ደንበኛው ግብር የያዝነውን መሬት እንደድኃው ገባር ልክ በያንዳንዱ ጋሻ ግብሩን ተካክለን እንገብር፡፡ ይኸንኑም ብናደርግ ከባላገሩ ላይ የከበደውን ታላቅ የግብር ሸክም መቀነስና ማቅለል ይቻላል፡፡ ገባሩም ግብሩ ከቀለለለት በመሬቱ መኖር ይችላል፡፡ ደግሞ በየጊዜው በየሻለቃው ምክንያት እንዳይጨመር መንግሥቱ የሚጠበቅበትን ደንብ ከሰራለት መሬቱን ለቆ የሚሄድ ገባር
ምንም ያህል አይገኝም፡፡ ግብሩም በሚሄድበት ስፍራ ሁሉ ተመሳሳይ ስለሆነ ይኸ የቀረበልን ነገር ትልቅ ነው፡፡ ዳር አገር በተባለው አገር ሁሉ ባላገሩ አቅም እያነሰው ነው እንጂ በዚህ በቀረበው አቤቱታ አይነት ወሬውን እንደምንሰማው ያልደኸየና
ያልተቸገረ አገር አይገኝም፡፡ ይኸውም በብርታት ቶሎ የሚድንበት ነገር ካልተሰራ፣ይኸ አሁን የተፈራው በላተኛ አገሩን ፈጽሞ ካደኸየ በኋላ የሚበላው ሲያጣ እንደገና
መንግሥቱን እያስቸገረ የከፋ ነገር ሳይሆን አይቀርም፡፡ አሁን እንኳን የተመቻቸው ሹማምንት አገር ሲለምኑ፤ 'ይኸ ያልተበላ አገር ነውና ስጡን' ይላሉ ይባላል››፡፡ ብዬ ነገሬን ጨረስኩ፡፡
#እዚያም ከነበሩት አንዳንድ ትልልቆች መኳንንት አዎ «ያዳሜን እርስት ሁሉ ልትነቅል፤ የማይሆነውን ነገር» እያሉ አንድ ጊዜ ነገራቸውን አወረዱብኝ፡፡ከልጅ እግሮቹ ወገን ግን አንዳንዶቹ ምንም ቢያንሱ፤ የኔኑ አይነት አሳብ የመሰለውን ተናገሩ፡፡ በዚሁ ስንጨቃጨቅ ያንለት ሰዓቱ ደርሶ ተለያየን፡፡ ሁለተኛም በዚህ ነገር የተነጋገርንበትንና የተፈጸመ እኔ የማውቀው የለም፡፡ እንደመሰለኝም ላቤት ባዮቹ መልስ ያህል ምንአልባት ጥቂት ነገር ያደረጉላቸው ይኖር ይሆናል፡፡
📌ካየሁትናከማስታውሰው፤ራስእምሩኃይለሥላሴ፤180-2
****
►ከዚህ ክስተት መገንዘብ እንደሚቻለው የኢትዮጵያ ገባሮች በምን ደረጃ ይጨቆኑና ይበዘበዙ እንደነበረ ነው። ትላልቆቹ መሣፍንት እና መኳንንቶች ለገባሮቻቸው ያላቸው ሀዘኔታ በእጅጉ ያነሰ እንደሆነ በወቅቱ ከፍተኛ መሣፍንት የነበሩትና የግርማዊ ጃንሆይ የቅርብ ዘመድ ከሆኑት ራስ እምሩ በላይ ምስክር የለም።ልዑል ራስ እምሩ ከመሣፍንቶች በሙሉ በተራማጅነታቸው የሚጠቀሱበትና ከደርግ ጅምላ ግድያ የተረፉበት ዋነኛ ምክንያት ይኸው ማንነታቸው ነው።