08/09/2020
የ2013 ዓ.ም ያሆዴ የሀዲያ ብሔር ዘመን መለወጫ ክብረ በዓል የኮሮና ቫይረስ ስርጭትና ተጋላጭነት ለመከላከል እንዲቻል እንደ ቀድሞ ህዝብ በተሰበሰበበት እንደማይከበር ተገለጸ፡፡
የሀዲያ ብሄር ዘመን መለወጫ ክብረ በዓል አከባበር የዞኑን ባህላዊ እሴቶችን ከማጠናከር አንጻር ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ከመሆኑም ባለፈ ባህላዊ ክዋኔው በቅርስነት እንዲመዘገብ እየተሰራ እንደሆነ የገለጹት የዞን ባህል ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሲሳይ እዉነቱ የ2013 ዓ.ም የበዓሉ አከባበር ሂደት ህብረተሰቡ ለኮሮና ቫይረስ ተጋላጭ በማይሆን መልኩ ሁሉም በያለበት ሊያከብር እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡
ሆኖም ግን ይህ ታላቅ በዓል ታስቦ የሚውልበትን እና የበዓሉ አከባበር ሂደት አስመልክቶ የዞን ባህል ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ከዞን፣ከወረዳና ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፍዎች ጋር እንዲሁም ከብሄሩ የባህል ሽማግሌዎች እና ሌሎች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በስፋት ወይይት የተደረገበት ሲሆን እንደ ቀድሞ ህዝብ ባልተሰበሰበበት እና የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ባገናዘበ ሁኔታ የክብረ በዓሉን ክዋኔዎች ባካተተ መልኩ እንደሚከበር ተገልጿል።
የሀዲያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሻናፊ ጴጥሮስ በበኩላቸው የብሔሩ ዘመን መለወጫ ክብረ በዓል እንደ ከዚህ በፊቱ ሁሉም የዞኑ ህብረተሰብ በአንድነት እንዲያከብር በወቅቱ የተጋረጠው የቫይረስ ስርጭት ጤና ስጋት በመሆኑ የሚደረገው የትኛውም የበዓሉ አከባበር ስርዓት ለቫይረሱ ተጋላጭ በማይሆን መንገድ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡
በዓል ለማክበር ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ የዞኑ ተወላጆች ባሉበት አካባቢ ሆነው እንዲያከብሩ ጥሪ አቅርበው ምን አልባትም በአስገዳጅ ሁኔታ የሚምመጡ ከሆነም በተዘጋጀው ለይቶ ማቆያ ገብተው ጤናቸው ሳይረጋገጥ ወደ ህብረተሰቡ እንደማይቀላቀሉ አሳስበዋል፡፡
ህብረተሰቡ የበዓሉን አቀባበር በተለያዩ የሚዲያ አማራጮች የሚከታተሉበት ሁኔታ እንደሚሰራ ተጠቁሟል።
ዘገባው የሀድያ ዞን መ/ኮ/ጉ/መምሪያ ነው።