12/08/2026
በወላይታ ህዝብ ዘንድ አራት አይነት ባህላዊ የዳኝነት ሥርዓቶች ያሉ ሲሆን እነዚህም፦
1ኛ - Awaasiya/አዋሲያ
2ኛ - Mahaa/ማሃ
3ኛ - Sigaa/ሲጋ
4ኛ - Cuucaa-Cachchaa/ጩጫ ጫቻ
በመባል ይታወቃሉ።
በነዚህ የዕርቅ ፍልስፍናዎች ውስጥ... ወላይታ የተሰበረ ልብን የሚጠግን ሀገር በቀል ጥበብ እንዳለው ትልቅ ማሳያ ነው።
በርግጥ የሰው ልጆች በአብሮነት በኖሩባቸው ዘመናት ሁሉ፣ አለመግባባቶችና ግጭቶች ተከስተው ማለፋቸው አልቀረም። ነገር ግን በዚህ ረዥም የሕይወት ጉዞ ውስጥ ብልሃት የማይለያቸው የወላይታ አባቶች፣ ለግጭቶችና ለአለመግባባቶች የሚሰጡት ምላሽ ሁልጊዜም የተለየና አስተማሪ ነው። አዋሲያ በሚባለው የእርቅ ስርዓት የሚከወኑ ሁነቶች ደግሞ እጅግ ያስገርማሉ።
የወላይታ ታሪክ አዋቂ፣ ደራሲና ተመራማሪ የሆኑቱ አቶ አዳነ አይዛ ስለ አዋሲያ እንዲህ ይላሉ፦
"አዋሲያ፤ ቀጭኑን የአብሮነት ሰንሰለት ሳይበጥስና ፍቅር ሳይሸረሸር ፍትሕን የማስፈን ነባር ሀገር በቀል የዕርቅ ፍልስፍና ነው።"
ይኼው... ከረዥም ዘመናት በፊት የተዘረጋውና "አዋሲያ" በመባል የሚታወቀው ሀገር በቀል የዕርቅ ሥርዓት ፍትሕን የሚያሰፍነው የማህበረሰቡን ቀጭን የአብሮነት ሰንሰለት ሳይበጥስና በመካከላቸው ያለውን ፍቅር ሳይሸረሽር ነው።
በዚህ ፍልስፍና ውስጥ የሚሰየሙ የሀገር ሽማግሌዎች ምህረት አልባ ብይን ከመስጠት ይልቅ፣ ለዘላቂ ሰላምና ለአንድነት ቅድሚያ ይሰጣሉ።
" #ከኖራችሁት ዕድሜ፣ #የምትኖሩት ይበልጣል" እያሉ የበዳዩን ገመና በአደባባይ ሳይዘረግፉ፣ የተበዳዩን ልብ አክመውና ጠግነው ዕርቅ የሚያወርዱበት መንገድ ከዘመናዊው የዳኝነት አካሄድ እጅጉን የተለየ ነው።
በአዋሲያ ሥርዓት የተጣሉ ባለትዳሮችን፣ ወላጆችንና ልጆችን አልፎም ወንድማማቾችን ከሚያለያያቸው ይልቅ የሚያስተሳስራቸው ነገር ይበዛል።
ዛሬ ላይ በየማህበረሰቡ ለሚታዩ የትዳር ፍቺዎችና ማህበራዊ ቀውሶች ዋነኛው መፍትሔ ቀላል ዕለታዊ ግጭቶችን ወደ ፍርድ ቤት ከመርታት ይልቅ፣ ጉዳዮችን በዚህ በአዋሲያ ሥርዓት መፍታት ነው።
አዋሲያ የቤተሰብ ጉዳይና ምስጢርን የመጠበቅ መርህ ስላለው፣ የተጣሉ ወገኖች ጉዳይ በአደባባይ እንዳይወጣና ክብራቸው እንዳይነካ ያደርጋል።
ዘመናዊው ሕግና ፍርድ ቤት ጥፋተኛን ይቀጣሉ እንጂ የተሰበረ ልብን አይጠግኑም፤ የሻከረ ግንኙነትንም አያድሱም፤ በመሆኑም ማህበራዊ ቀውሶችን በዘላቂነት ለመፍታትና ፍቅርን ለማስቀጠል እንደ 'አዋሲያ' ያሉ ሀገር በቀል የጥበብ መንገዶችን መከተልና ማልማት የዘመናችን ብልህነት ነው።