30/11/2025
ማሩ ቀመስ ደምቢያ ደብረ ሲና ማርያም ተገኘን !!
(ታዴ የማመይ ልጅ )
| ተወዲያ ከውቢቷ ባሕር ዳር እስከ ታሪካዊቷ ጎንደር፤ ከለምለሙ የጎጃም ምድር እስከ ማማው በጌምድር የተዘረጋው የጣና ሐይቅ ከሕዋ ላይ ሆነው ሲያዩት የሰውን ልጅ ❤️ የልብ ቅርጽ ገፅታ ይዞ ይታየኛል ።
ከዘጌ እስከ ጣና ቂርቆስ፣ ከደልጊ እስከ ሬማ መድኃኒዓለም፣ ከክብራን እስከ ጀበራ ማርያም፣ ከእንጦስ እስከ ማንዳባ፣ ከጉረር እስከ አንጋራ ከቁንዝላ እስከ ጎርጎራ እና ሌሎችም የተንጣለለዉን ሐይቅ ጉማራ ጉዛራና ርብ የተባሉ አፍላጎች ሰርክ ይገብሩለታል ።
ለማንቻዉም በጣና ሃይቅ ወደብ፤ በቤጌምድር መደብ በጎንደር እናት ባሕላዊ፣በቅዱሳን መኖሪያ፣ የበረከት ማደሪያ፣ የእውቀትና የጥበብ መፍለቂያ፣ መንፈሳዊና ሞራላዊ ሃብቶች መጠለያ ፣ለዘመነ መሳፍንት ማክተም ምክንያት ከሆኑ ቦታዎች አንዱም ነው፤ ማሩ ቀመስ ደንቢያ ዉስጥ ነኝ ፡፡
መዳረሻዬ ደግሞ ከረጂም ዘመን ጀምሮ እስከዛሬ በተዘረጋዉ ታሪኳ በዋሻዎቿ የሰው ልጅ ይኖርባት እንደነበር የሚነገርላት ፣ከህገ ልቦና እስከ ህገ ኦሪት፣ ከንጉሰ ነገስት እስከ ወታደራዊ መንግሥት፣ ከጥንታዊው እስከ ዘመናዊው፣ ከተዘመረለት እስካልተዘመረለት ፣የኢትዮጵያ የረጅም ዘመን ታሪክ በሚነገርበት፣ ስርዓተ ክህነት እና ስርዓተ መንግሥት የጸናባት ጎርጎራና የ704 ዓመቷ ደብረ ሲና ማርያም ገዳም ናት ፡፡
ከዚያ በፊት ግን ስላለሁበት ለጥ ያለዉ የደምቢያ ምድር ጥቂት ልበል አሁን የምገኝበት ስፍራ በኢትዮጵያ ታሪክ ያላስተናገደው ሁነት የለም ፡፡
አፄ ሱስንዮስ ኢትዮጵያ የሮማን ሐይማኖት እንድትቀበል አዋጅ ያስነገሩት ከዚህ ስፍራ ነዉ።
የአፋሩ ጦረኛው አህመድ ኢብን ኢብራሂም አልጋዚ …ግራኝ አህመድ ከርቀት የሰማዉ ገናናው ስሟን አይቶ ለመናገሻነት መረጦ በረሃውን አቋርጦ ለህልሙ መሳካት ከአስር አመት በላይ የተይከራተተላት በመጨረሻም አፈሯን ቀምሷል።
ግራኝ አህመድ መርጦ ጣና ዳርቻ ዋና መዲናውን ለማድረግ እንዳሰበ ሁሉ፤ ፋሺሽት ጥሊያንም ጎርጎራን እና ደንቢያን ዋና መናገሻው ለማድረግ ዳድቶት ነበር አሉ፡፡
ሐማሴኖች ትናንታችን የዘር ሀረጋችን ከዚህ ይመዘዛል ይሉናል ፣ዮዲት ጉዲትም መዲናዋ ለማድረግ መርጣታለች ፣ የዘመናዊቷ ኢትዮጵያ አንጥረኛ እና ጥበበኛ የሆኑት ቋረኛው ንጉስ የመሪነት ጥበብ ስንቃቸውን የቋጠሩት፣ የታላቅነት ራዕይ ህልማቸውን የወጠኑባት ማሩ ቀመስ ደንቢያ ነበር ፡፡
ስፍራው ከአፄ አምደ ፅዮን እስከ ታላቁ ንጉስ ሰርፀ ድንግል፣ ከ አፄ ፋሲል እስከ አፄ ሱስንዮስ ፣ከእንግሊዝ ተስፋፊዎች እስከ የፖርቹጋል አሳሾች ከሮም ቀሳውስት እስከ የግሪክ መልዕክተኞች ፋሺሽት ጣሊያን እስከ ሚሲዮናዊያን ከአፄ ኃይለ ስላሴ እስከ ኮሎኔል መንግስቱ እልፍ ታሪኩን በአጭር ቃላት ገልፀን መጨረስ አያስችልምና ቀጥታ ወደዛሬዋ መዳረሻዬ ላቅና ።
ይህ ሥፍራ በቅዱሳን መኖሪያ፣ የበረከት ማደሪያ፣ የእውቀትና የጥበብ መፍለቂያ ፣ ትናንት ጥበብ የተቀዳበት ፣ ዛሬም የሚቀዳበት ጥበብን የሚሹ ሁሉ የሚረኩበት ስለመሆኑ ሞገሱ ያሳብቃል ።
አሁን የምገኘው ከጎንደር ከተማ በስተምዕራብ 61 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ጣና ሀይቅ ዳር ነዉ ።
በስተምስራቅ የተንጣለለው ሐይቁ በማዕበል ይወዛዋዛል፡፡ ዛፎች ለጌታቸው ምስጋና የሚያቀርቡ ይመስላሉ፡፡ ጎንበስ ቀና ሲሉ አጀብ ያሰኛሉ፡፡ አበው መነኮሳት ስጋዬን ለመነኩሴ ነብሴንም ለስላሴ ብለው ሳያርፉ ለአገልግሎት ይፋጠናሉ፡፡ ስጋቸውን እያስራቡ ነብሳቸውን ይመግባሉ፡፡ ስለ ዓለም ሀጥያት፣ ስለ ምድር በረከት፣ ስለ ኢትዮጵያ ፅናት፣ ስለ ሕዝቦቿ አንድነት ሳይሰለቹ ይማፀናሉ፡፡
በሃ