11/07/2026
ባህርዳርን የፈተኗት "ጎጠኞቹ" በቃችሁ ይባሉ!!
ያለፉት አመታት ባህርዳር ላይ የነበረው ትግል ከተማዋ ከተፈጥሯዊ ወዟ ውጪ ሰርቶ የሚለውጣት መሪ አላገኘችም የሚል ነበር። የባህርዳርን የትናንትና የዛሬ ለውጦች ለማየት በትነሹ አይንን መግለጥ በቂ ነው። ከተማዋ በሶስት አመታት ውስጥ መሰረታዊ ወደሚባል ከፍታ ተሻግራለች። ይህ ከፍታ ያለፈበት ሂደት በዛሬ ውጤቱ ብቻ የሚለካ አይደለም። ይልቁንም ደም የተከፈለበት ውጤት ነው። ይህንን ዘርዘር አድርጎ ማየት ይገባል።
ከጥይት ድምፅ መናኸሪያነት ወደምቹ ከተማነት
ከተማዋ እንደሌላው የክልሉ አካባቢ ሁሉ የሰላም እጦት ወላፈኑ የገረፋት ነበረች። የክልሉ የፖለቲካና ኢኮኖሚ የስበት ማዕከል በመሆኗ ምክንያትም ተደጋጋሚ ሰላሟን የማደፍረስ ሙከራዎች ነበሩ። የከተማ አስተዳደሩ ይህንን ከመሰረቱ ቀይሯል። በ12:00 ሰዓት ሰው አልባ ይሆኑ የነበሩት የባህርዳር አስፓልቶች ዛሬ ሌሊቱን ሙሉ ሰው ይንቀሳቀስባቸዋል። የሌሊት የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዋ እየተመለሰላት ነው። ይህ እንዲሆን ብዙ ዋጋ ተከፍሏል።
በፖለቲካ ሸፍጥ የተሸፈነው ውምብድና
በከተማዋ ውስጥ ሰርጎ ገብቶ የለየለት ውምብድና ላይ የተሰማራ ሀይል ሰውን እያገተ፣ እየዘረፈና እየገደለ በራሱ የፕሮፖጋንዳ ክንፍ በኩል ደግሞ ከተማዋን መንግስት አልባ ለማስመሰል ጥሯል። እንዲህ ያለውን የተደባለቀ ሴራ ለመቁረጥ ብዙ ርቀት ተሂዶ እንዲመክን ተደርጓል። የባህርዳር መሪዎች እንዲህ ያለውን ርምጃ በመውሰዳቸው ሊመሰገኑ ይገባል።
የማይካዱ እውነቶች
👉የከተማ ልማትን ከዲሽ ቦይና ኮብል ድርደራ እሳቤ አውጥቶ ግዙፍ ፕሮጀክቶች እንዲጀመሩ አድርጓል። በዚህም በርካታ ደረጃቸው የተጠበቀ የአስፓልት መንገዶችና ማስዋቢያዎች ተገንብተዋል።
👉የትራንስፖርት ችግርን ለመቅረፍ አዳዲስ ባሶችን ከመግዛት እስከስምሪት ቁጥጥርና ማስተካከያ ድረስ ተሰርቷል።
👉የግለሰብና የቡድን ጥያቄ ያላቸውና በተጓተተ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግር ይሰቃዩ የነበሩትን እያደመጡ፣ እየመዘኑና እየወሰኑ ችግሩን ለመፍታት ተሰርቷል።
👉የክፍለ ከተማና የመምሪያ ተቋማት ላይ ከፍተኛ መሻሻል መጥቷል።
👉የመንግስት ሰራተኞች ቤት መስሪያ ቦታ የመስጠት ሂደት፣ የኢንቨስትመንት መፋጠን፣ ወደልማት ያልገቡ ፕሮጀክቶች ርምጃ፣ ድለላን ከመንግስት መዋቅር የማራቅ ጅምሮች....እነዚህ ከበጣም ጥቂቶች ናቸው።
እነ ካልበላን እናፍስሰው ቡድን
የባህርዳር ከተማ ዋነኛ ጋንግሪኖች የሷን ወተት እየጠጡ የጠገቡ ቁንጣናሞች ናቸው። የከተማው አመራር ሊወቀስ የሚችልበት አንዱ ችግር እነዚህን ግለሰቦች ተሸክሞ መቀጠሉ ነው። ከመንደራቸው አሻግረው መመልከት የማይችሉ ደካሞች የከተማዋን አመራር በተለይም ከንቲባ ጎሹ እንዳላማውን በሐሰት እየወነጀሉ ለማድከም በሙሉ አቅማቸው እየሰሩ ነው። በአስተባባሪ አመራርና በካቢኔ ውስጥ ተቀምጠው ውሳኔዎችን እነአያሌው መንበርን ለመሰሉ በጎጥ ለተከራዩአቸው ግለሰቦች የሚሸጡ ከሀዲዎች የከተማ አስተዳደሩ ፈተና ናቸው። እዚህ አካባቢ በክልሉም ሆነ በከተማው ላይ የሚስተዋል አጉል የማባበል አካሄዶች መታረም አለባቸው። እነዚህ ግለሰቦች የከተማውም የክልሉም ስጋት ናቸው። ከአማራነት የአንድነት ቅንፍ ወጥተው አይናቸውን በጎጥ ፎጣ የሸፈኑ ሰነፎች ከአሜሪካ እስከ ኡጋንዳ ከእስራኤል እስከ አውስትራሊያ በተዘረጋ የክፋት ገመዳቸው የባህርዳርን አመራር ለመጥለፍ ደጋግመው ሞክረዋል። ሆኖም እየታወቀ በመቻል ለማለፍ ተሞክሯል። ይህ ግን እዚህ በላይ እንዲጓዝ መፍቀድ ተገቢ አይደለም። ተቆራርጦ ከመዋቅሩ እየነቀሉ መጣል ይገባል።