02/06/2026
ዳኤ ሁሉሽም ወደተግባር : ኢትዮጵያን ወደ ተምሳሌት ሀገር
የዲላ ከተማ የአስፓልት እና የኮሪደር ልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ አበባየሁ ታደሴ (ዶ/ር) አሳሰቡ
ዲላ፡ግንቦት፣25/2018ዓ.ም (ጌዴኦ ቴሌቪዥን)
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በዲላ ከተማ አስተዳደር የታቀዱ የአስፋልት እና የኮሪደር ልማት ግንባታ ሥራዎች ይበልጥ ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አበባየሁ ታደሴ (ዶ/ር) አሳሰቡ።
ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በዲላ ከተማ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎችን የገመገሙ ሲሆን በቀጣይ ልዩ ትኩረት በሚሹ ጉዳዮች ላይም ከባለድርሻ አካላት ጋር የጋራ ውይይት አካሂደዋል።
በውይይቱ ላይ አበባየሁ ታደሴ (ዶ/ር) እንደገለጹት እስካሁን ባለው ሂደት በተቋራጩ በኩል የተደረገው ቅድመ ዝግጅትና ለአስፋልት ግንባታ የሚውል የኮንስትራክሽን ግብዓት አቅርቦት አፈጻጸም መልካም የሚባል እንደሆነ አንስተዋል።
በከተማዋ የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ሥራዎች የዲላን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለሕዝቡ ያላቸው ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ የጎላ መሆኑን ምክትል ርዕሰ-መስተዳድሩ ጠቅሰዋል።
በመሆኑም እነዚህ የልማት ሥራዎች በሚቀጥሉት ጊዜያት በፍጥነትና በጥራት መከናወን እንዳለባቸው አሳስበዋል።
ለዚህም ከክልሉ ዲዛይንና ሱፐርቪዥን ኢንተርፕራይዝ ጋር በጋራ በመሥራት ግንባታዎቹ በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ተጠናቀው ለሕዝብ አገልግሎት ክፍት መሆን እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዲዛይንና ሱፐርቪዥን ኢንተርፕራይዝ ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር አብድሳ ኩፎ በበኩላቸው የአስፋልትና የኮሪደር ልማት ሥራዎቹ በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቁ ለማድረግ ተቋማቸው የበኩሉን ኃላፊነት እንደሚወጣ አረጋግጠዋል።
ኢንተርፕራይዙ የተጣለበትን የማማከር፣የቅርብ ክትትልና የቁጥጥር ሥራ በትጋት እንደሚወጣ ሥራ አስኪያጁ አስታውቀዋል።
የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ መስፍን ደምሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው የከተማ አስተዳደሩ ፕሮጀክቶቹ ያለምንም መስተጓጎል በተቀመጠላቸው የጥራት ደረጃ እንዲጠናቀቁ አስፈላጊውን የቅርብ ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግ ከንቲባው አረጋግጠዋል።