
01/06/2025
በሚዛን አማን ከተማ ዛሬ ማለዳ የከተማ አስተዳደር አመራሮችን ጨምሮ ህብረተሰቡን ያሳተፈ የፅዳት ዘመቻ ተካሂዷል
ሚዛን አማን ግንቦት 23/2017 ዓ/ም በሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ተከታታይነት ያለው የጽዳት ዘመቻ በማካሄድ ከተማዋን ውብና ማራኪ ለማድረግ የሚያስችል የጽዳት ዘመቻ ስራ በዛሬው እለት ተጀመረ።
የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጅነር ሰለሞን ሌዊ እንደተናገሩት የከተማዋን ፅዳት በዘላቂነት ለመጠበቅ በመንግሰት አቅም ብቻ ሳይሆን የሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ንቁ ተሳትፎ እንደሚያስፈልግ ገልፀዋል
በዚህም የከተማዋ እያንዳንዱ ነዋሪ አካባቢውን በ20 ሜትር ርቀት ፅዳቱን መጠበቅ እንዳለበት አብራርተዋል።
አሁን ላይ በከተማ አስተዳደሩ እየመጣ ያለውን ፈጣን ዕድገትና ለውጥ ይበልጥ ለማስቀጠል የሚያስችል ሰፋፊ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች እያከናወነ መሆኑን ከንቲባው ተናግረዋል
በተለይ ባላለፉት ዓመታት የከተማዋን ፅዳት ለመጠበቅና ህብረተሰቡ የፅዳቱ ባለቤት እንዲሆን በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን የገለፁት ከንቲባው በቆሻሻ የተደፈኑ ዲች ቦዮችን በመክፈት የማፅዳት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል።
በየሳምንቱ በሚካሄዱ የፅዳት ንቅናቄ ስራዎች ብቻ የአካባቢ ፅዳት አይጠበቅም ያሉት ከንቲባው ማህበረሰቡ ፅዳትን ባህል አድርጎ የአካባቢን ፅዳት ማስጠበቅ ላይ ንቁ ተሳትፎ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።
አካባቢያችንን ማፅዳት ብቻ ሳይሆን ዳግም የቆሻሻ መጣያ ቦታ እንዳይሆኑ ነዋሪው በባለቤትነት መጠበቅ ይኖርበታልም ብለዋል::
የከተማ አስተዳደሩ ዋና ማዘጋጃ ቤት ኃላፊ ኢንጅነር በረከት ምናሴ በበኩላቸው በከተማዋ የፅዳት፣ የውበት እና አረንጓዴ ልማት ስራዎች በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
በከተማዋ ያለውን የቆሻሻ አወጋገድ ስረአት በተገቢው መልኩ መሆን እንዲችልና ብዙሀኑ ያፀዳውን ጥቂቶች ማቆሸሸ ስለማይገባቸው በህግ ተጠያቂ የማድረጉ ተግባር በቀጣይ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።
ከተማን ፅዱና ውብ ለማድረግና ቆሻሻ የአካባቢን ገፅታ እንዳያባላሹ ለነዋሪው ህብረተሰብ በባለቤትነት እንዲጠብቁ የማስተላለፍ ስራዎች እየተሰሩ እንደሆነም አብራርተዋል።
በፅዳት ዘመቻው የተሳተፉ አመራርና የከተማው ነዋሪዎችም ከተማውን ውብና ፅዱ ለኑሮ ምቹ ለማድረግ የተጀመረው ስራ የሚበረታታ መሆኑን ተናግረው ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
በተካሄደው የፅዳት ዘመቻ ላይ የሚዛን አማን ከተማ ከንቲባ ኢንጅነር ሰለሞን ሌዊ፣ የከተማ አስተዳደሩ ብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ሃላፊና ዋና የመንግስት ተጠሪ አቶ ተስፋዬ ጊስካርን ጨምሮ ሌሎች የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊዎች ሆነዋል።